2013 ሴፕቴምበር 22, እሑድ

‹አንበሳው› ማን ነው፤ ‹አህያውስ› የምን ምሳሌ?

   የታወቀ ነው፤ የተለመደ! በየተረቶቻችንና ሥነ-ቃሎቻችን አንበሳ መሪ ተዋናይ ነው፤ ያለእሱ መድረኩ አይደምቅም፤ ምልልሱ አይሞቅም፤ በተቃራኒው ደግሞ አህያን ረዳት ተዋናይ አድርገን ልንቆጥረው እንችላለን፤ ቢኖር ያገለግላል ባይኖር ደግሞ ብዙም አያጐድል ተብሎ ችላ የሚባል፡፡

ይኼ መጣጥፍ በሕይወት መድረክ ላይ ሁለቱንም ሆነን የመተወን እድል ስለገጠመን ሰዎች ለመተረክ የሚሞክር ነው፤ አንበሳ ሆነን ወይም ተብለን በህይወት ሳለን ስለተፈራን ሞተን ስንገኝ ደግሞ ሐውልት ስለቆመልን ሰዎች፤ አህያ ሆነን ወይም ተብለን በህይወት ሳለን በጫንቃችን ላይ ውርደት በጭንቅላታችን ላይ ስቅየት ስለተፈራረቀብን፤ ሞተን ስንገኝ ደግሞ ለማንም ጥንብ ጐታች ስለምንሰጥ ሰዎች የሚተርክ…
እውነት ነው አንበሳ መሆን ደስ ይላል፤ ‹ሞኣ አንበሳ ዘእምነገደ ይሁዳ…› መባል ደስ ይላል፤ አንበሳ ምሳሌነቱ ከድሮ ጀምሮ ለተወደደ እና ለተከበረ ነገር ነው፤ ኢየሱስም ከይሁዳ ዘር ነው ብለን ዘር ማንዘሩን እንቆጥራለን፤ ከአንበሳው ወገን የሚመደብ! እናም የፊተኞቹ ነገሥታት ‹አንበሳነት ከጥንት ጀምሮ በደማችን የተዋኸደ ነው› ለማለት፤ የተቀደሰውን ነገር ‹ያደግንበት ነው› ለማለት፤ ‹ሞኣ አንበሳ…› ይላሉ፤ መጽሐፍ ቅዱስ በአንድ በኩል አንበሳን እንዲህ ለተባረከ ነገር አሳልፎ ሲሰጠው፤ በሌላ ምዕራፍ ላይ ደግሞ አንበሳን በዲያብሎስ ይመስለዋል፤ በነጣቂ፣ በአስጨናቂ፣ በእንቅልፍና በእረፍት ሰራቂ!
እናም እንዲህ እላለሁ፤ የሀገራችንና የአሕጉራችን ቀደምትና የአሁን መሪዎች ‹አንበሳ›ነን ብለው ራሳቸውን ሲመስሉ የትኛውን ዓይነት አንበሳ ሆነው አግኝተናቸዋል?
…ከቅዱሳት መጽሕፍት ውጪ፤ አንበሳ በየተረቱ ውስጥ ድል አድራጊ ነው፤ አንድም አውሬ እፊቱ ይቆም ዘንድ አይቻለውም፤ ‹ንጉሥ› ነው፤ ቀጪ እና ተቆጪ የለውም፤ ንዴቱ ዛፎቹን ያንቀጠቅጣል፤ ተራሮችን ያርዳል፤ እጁ ውስጥ ከገባን ከመዳፉ ፈልቅቆ የሚወስደን ሃይል ማን ነው?... በርግጥ ይህ ሁሉ ሃይል አንበሳው ስልጣን ላይ እስካለ ነው፤ ስልጣኑ የሚጠናቀቀው ደግሞ የጉብዝና ወራቱና የወራት ዘመኑ ሲያከትም ነው፤ ከዚያ በኋላማ፤ ዝንቦች መጫወቻ ያደርጉታል፡፡

2013 ሴፕቴምበር 20, ዓርብ

እጃችሁ በደም ተነክሩዋል….



እጃችሁ በደም ተነክሯል….
…ወደ ኦሪታውያኑ ዘመን ልመልሳችሁ፤ ከዚያ ዘመን ውስጥ ፈርኦንን፣ ሙሴንና ኢያሱን እናንሣ፤ እነዚህን ሰዎች ደግሞ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ እንፈልጋቸው፤ የእነዚህ ቢጤዎች ናቸውና ዛሬ እንደጨቋኝ ገዢ ተቆጥረው የወቀሳ ናዳ የሚዘንብባቸው፤ የእነዚህ ቢጤዎች ናቸውና ዛሬ ከጭቆና ነፃ እንዳወጡን ተነግሮ የሰማዕት ሀውልት እንዲቆምላቸው የሚደረገው፤ የእነዚህ ቢጤዎች ናቸውና ዛሬ በህይወት ኖረው÷ ከወንድሞቻቸው የተቀበሉትን የትግል ዓርማ ከፍ አድርገው የተስፋይቱን ምድር እንዲጐበኙ የፍትህ አምላክ ስለ ፈቀደላቸው ደስ የምንሰኝባቸው!
…‹ያ› የምንለው ትውልድ ተገልጦና ተነብቦ የማያልቅ መጽሐፍ እየሆነ ነው፤ ውለን ባደርን ቁጥር ተድበስብሰው የታለፉና ተቆፍረው የተቀበሩ ጉዶችና ገድሎችን እያደመጥን ነው፤ ያንን ትውልድ የሚያጀግኑ መዝሙሮች መስማት ብቻ ሳይሆን፤ የትውልዱን አካሄድ የሚነቅፉ ብዕረኞችም በየህትመት ሚዲያው ብቅ ብቅ እያሉ ነው፤ እነዚህ ብዕረኞች ትውልዱን ጀብደኛ ነበረ ነው የሚሉት፤ ከውጭ ሀገር የተኮረጀ ርዕዮት ይዞ ስለተነሣ ነው ተሰናክሎ የወደቀው ነው የሚሉት፤ ሕዝቡ የኔ ነው ብሎ የሚያምንበትን አምላኩን ከልቡ ለማስወጣት ይታገል ነበር ነው የሚሉት፤ ብዙ የሚሉት ነገር አላቸው፤ እንዲህ በማለታቸው አንዳንድ የያ ትውልድ አባላት ተቺዎቻቸውን ተቆጥተዋል፤ ሣታውቁን ነው የምትዘባርቁት ብለዋል፡፡
          ጉዳዩ አጨቃጫቂ ነው፤ ክርክርና ንትርኩም የሚቀጥል! ያ ትውልድ ሜዳው ሰፊ ነው፤ በዚህ ሰፊ ሜዳ ላይ በ1960ዎቹና 70ዎቹ መጀመሪያ የነበሩ ወጣቶች ተጋጥመውበታል፤ ተጋጣሚዎቹ የማይከሰስና የማይወቀስ የሆነውን ንጉሳዊ አገዛዝን ገርስሰው ጥለዋል፤ የማይነካውን ከደፈሩ በኋላ ግን እርስ በርስ ተበላሉ፤ እርስ በርስ ተዋዋጡ፤ አብዮቱ ‹አፋጀሽኝ›ን ሆነ፤ መቧደናቸው ቀጠለ፤ ሞት፣ ስደት እና እስር የሁሉንም ቤት ለመጐብኘት ትጥቁን አጠበቀ፤ ደርግም፣ ኢሕአፓም፣ ሕወሓትም፣ መኢሶንም… ወዘተርፈው በሙሉ ልቡን ወያኔ አደረገ፤ ሸፈተ፤ ከተማውም ገጠሩም ዱሩም ገደሉም የእዚህ ትውልድ መሸሸጊያ ሆነ…

2013 ሴፕቴምበር 19, ሐሙስ

ያልተቀበልናቸው (2)



ይኼ የ ‹ያ ትውልድ› ውጤት ነው፤ ከ1950ዎቹ ወዲህ (ከታህሳስ ግርግር በኋላ) በተፈጠረው የፖለቲካ ትኩሳት ሰበብ፤ እነ ጥላሁን ገሠሠ (ድምፃዊ) ለመጀመሪያ ጊዜ ከአማርኛ ቋንቋ ውጪ አይደፈር የነበረውን በኦሮምኛ ቋንቋ ዘፍነው በሸክላ አስቀረፁ፤ እነ መኃሙድ አህመድ (ድምፃዊ) የጉራጊኛ ዘፈን አስደመጡ፤ ቀስ በቀስ ሌሎች ተከተሉ፤ አፍ መፍቻ ቋንቋቸው አማርኛ ያልሆነ ደራሲዎች መነበብ ጀመሩ - ጸጋዬ ገ/መድህን ከአምቦ÷ ስብሃት ገ/እግዚአብሔር ከአድዋ÷ ሰሎሞን ደሬሣ ከወለጋ÷ ሳህለሥላሴ ብርሃነማርያም ከእምድበር÷ አማረ ማሞ ከሲዳሞ… በኢህአዴግ ዘመን ደግሞ አንዱን ብሄር መርጦ፣ አንዱን ማኅበረሰብ ለይቶ ራሱንም የተዘፈነለትን አካባቢም የሚያስተዋውቅ ድምጻዊ በዛ፤ ዘፈኖቹ በአብዛኛው ተመሳሳይና ተደጋጋሚ ይዘት ያላቸው (የሆነ ሰው፣ የሆነ ቦታ ሄዶ፣ የሆነች ሴት ዓይቶ፣ በፍቅሯ ተማርኮ ‹አንቺን ካገኘሁ አዲስ አበባ ለምኔ› የሚሉ፤ ከግጥሙ ይዘት ይልቅ ለአጨፋፈር ስልታቸው ቅድሚያ የሚሰጡ) ቢሆኑም፤ የተጫወቱት ሚና እና ሚዲያው የሚሰጣቸው ሽፋን ቀላል አይደለም፡፡ የኦሮሞዎች ‹እሬቻ›ን፣ የሲዳማዎች ‹ጨምበላላ›ን፣ የትግራይ ክልል አካባቢ ነዋሪዎችን ‹ሻደይ›ን ማክበራቸውም ጥሩ ነው -
 እዚህ ደረጃ ለመድረስ ጥርጥር የለውም ብዙ ዋጋ ተከፍሏል፤ ሆኖም ግን ነጠላ ዜማ ስለተለቀቀለትና አንድ ትውፊታዊ በዐሉ ስለተከበረለት አንድ ብሄር ማንነቱ ታወቀለት ማለት አይደለም፤ ይሄ ብቻ በቂ አይደለም፤ ማንነት በዳንስ ብቻ አይለካም፤ በብሄር-ብሄረሰቦች ቀን እንዲታደሙ ስለተጋበዙ ብቻ ሙሉ ማንነታቸው ታውቆላቸዋል ማለት ስህተት ነው፤ ማንነት በጥልቀት የሚታይ መሆን አለበት እንጂ፤ እንደ ብሄራዊ ቴአትር ባለ አገር ፍቅር መድረክ አኗኗራቸው በጨረፍታም ቢሆን የሚታይ መሆን አለበት እንጂ፤ እንዲሁ ስለተዘፈነላቸውና ዳንስ ማሳያ መድረክ ስለተዘረጋላቸው የችግሮቻቸው ቀዳዳ ተደፈነ ማለት አይደለም፡፡

2013 ሴፕቴምበር 4, ረቡዕ

መክሊታቸውን ለቀበሩ



1
እንደመድሀኒት አዋቂ ነን
የየሙያችን ’ኤክስፐርቶች’።
ለቤታችን አጥር ሰርተን፤
ለልባችን አጥር ሰርተን፤
ለዕውቀታችን አጥር ሰርተን፤
ዙሪያችንን በሾህ አጥረን
አልፎ ሂያጁን ተጠራጥረን
ከኮራጅ መሳይ ዕውቀት አሳሽ
ምስጢር ወሳጅ የልብ ወዳጅ
በር ዘግተን
ደጅ ቆልፈን
ያለን፤ እንደ መድሀኒት አዋቂ ነን!
2

በተክርስቲያንም - ቤተ እስልምና

2013 ሴፕቴምበር 3, ማክሰኞ

ከጥቁር ሰማይ ስር



ጥዋት ጥዋት፣ ወደ ቢሮ ለመሄድ - መታጠፊያው ጋ ሲደርስ - እተለመደ ቦታዋ ቁጭ ብላ የሚያጉተመትም በሚመስል ድምጿ ያለማቋረጥ ስታወራ ይሰማታል፡፡ የአራት ልጆች እናት የሆነችዋን የኔ ቢጤ፡፡
የእናታቸውን ያህል ባይሆንም ጎስቁለዋል፡፡ እንደ ምጣድ ማሰሻ የቀድሞ ከለሩ ያልታወቀ ከነቴራ ለብሰዋል - ከወገባቸው በላይ፡፡ ከመሃከላቸው አንዳቸውም ቃጭል አንጠልጥለው አልተወለዱም፡፡
. . . በማያውቀው ቋንቋ ታወራቸዋለች፡፡
ልጆቿ አይመልሱላትም፡፡ እርስ በርሳቸው ሲጨዋወቱ በአዲስ አበባ አማርኛ ነው የሚግባቡት፡፡
እንዲህ በከንቱ ጉንጭዋን የምታለፋው በውስጡ ያደረውን ጩዋሂ መንፈስ ላለማዳመጥ ይሆን? ብሎ ያስባል
ጤንነቷን የማይጠራጠር የለም፡፡ አንዳንዶች ፥ ስለ ልጆቿ የወደፊት ዕጣ ፈንታ ማሰላሰል ስታበዛ ይሆን ያተሳሰብ ማዛንዋ የተዛባው? ይላሉ፡፡
ሁልጊዜ ያልተለመደ ነገር ስታደርግ ያጋጥመዋል፡፡ እጇ ላይ የተገኘን ማንኛውም ነገር ለአራት አካፋፍላ ለልጆች ታድላቸዋለች፡፡ ለራሷ የምታደርገው አይኖራትም፡፡ ከሲታ ናት ደግሞ፤ ያለ እህል ውሃ ለመኖር ሙከራ የጀመረች እስኪመስል ድረስ፡፡
ሳንቲም ተወርውሮ እግሯ ስር ያረፈ እንደሆነ ቅጭልጭልታውን ሰምታ እንኳን ቀና አትልም፡፡ ማንንም አይታይም - አገጯን ጉልበቷ ስር ደብቃ ነው፤ ቀኑን ውላ የምታመሸው፤ የምታነጋውም! መንገድ ዳር፡፡

2013 ኦገስት 29, ሐሙስ

2013 ኦገስት 28, ረቡዕ

ያልተቀበልናቸው…(ክፍል 1)


ያልተቀበልናቸው…(ክፍል 1)

…ኢትዮጵያ ውስጥ እያሉ፤ ኢትዮጵያዊ እየሆኑ፤ እንደውጭ ዜጋ የምንቆጥራቸው አሉ፤ እንደ ውጭ ዜጋ ባንቆጥራቸውም ‹የእኛ ናቸው› ብለን አምነን ለመቀበል የምንቸገርባቸው አሉ - ከእነዚህ ብሄሮች ወይም ማህበረሰቦች ጋር አንድ ማዕድ አንቀርብም፤ ከብቶቻቸው ከከብቶቻችን ጋር አይውሉም፤ በጋብቻ ተዛምደን አጥንታቸው ከአጥንታችን ደማቸው ከደማችን ጋር አይዋሃድም፤ አልተቀበልናቸውም -ልክ እንደ መጻተኛ - ልክ እንደ ባይተዋር - ልክ እንደ ድንገተኛ እንግዳ - የሚታዩ ሆነዋል፡፡ ሀገሪቷ ከህጋዊ ባሏ ያልወለደቻቸው ይመስል ሳቅና ለቅሶዋን ከተቀሩት ልጆቿ እኩል የማይካፈሉ የሚመስለን፤ ውለታ የማያኖሩላትና ብድር የማይከፍሉላት የሚመስለን፡፡ ሳናውቃቸው፣ ሳንቀርባቸው፣ ሳንጠይቃቸው የሚያልፍ - ጥላ መስለው፣ ጥላ ለብሰው፡፡